Friday, August 22, 2014

በሰሜን ጎንደር ዞን አለፋ ወረዳ የሚገኙ አርሶ አደሮች በገዥው ስርዓት ወርሃዊ መቆጣጠሪያ ተብሎ የወረደውን መመሪያ በመቃወም ላይ እንደሚገኙ ለማወቅ ተችሏል።



የኢ.ህ.አ.ዴ.ግ ስርዓት ባለስልጣኖች የስልጣን እድሜያቸውን ለማራዘም የሚያገለግል ወርሃዊ መቆጣጠሪያ አውጥተው በልማት ቡድንና በህዋስ ቡድን አደረጃጀት በሚል የወረዳውን አርሶ አደሮች አንድ ለአምስት እንዲደራጁ ያወረዱትን መመሪያ ተግባራዊ እንዲያደርጉ የተመደቡ ባለሙያዎች በህዝብ ተቀባይነት ባለማግኘታቸው ለአፈፃፀም ተቸግረው እንዳሉ ምንጮቻችን በላኩት መረጃ ታውቋል።
  መረጃው ጨምሮም የአለፋ ወረዳ ነዋሪ ህዝብ ከክልል ጀምሮ እስከ ቀበሌ የሚገኙ አስተዳዳሪዎች የሚከተሉት አሰራር ለራሳቸው ብቻ እንጂ የህዝብን ኑሮ ግምት ውስጥ ያስገባ ባለመሆኑ የልማት ቡድንና የህዋስ ቡድን አደረጃጀት እያሉ በአዝመራ ወቅት በስብሰባ ጠምደውን ይውላሉ በማለት ምሬታቸውን እየገለፁ መሆናቸውን አስረድቷል።