Tuesday, September 30, 2014

በኦሮምያ ክልል በመንግስት ትምህርት ቤቶች የሚሰሩ መምህራን ያለፍላጎታቸው ከመስከረም 4/2007 ዓ.ም ጀምረው ስብሰባ ላይ ተጠምደው እንደሰነበቱ ምንጮቻችን ከቦታወ ገለፁ።



በምንጮቻችን መረጃ መሰረት በኦሮምያ ክልል በአምቦ ዞን ስልኪ አምባ ወረዳ የሚገኙ መምህራን በገዥው መደብ ተገደው የኢህአዴግን እስትራቴጂና የድርጅቱን የኋላ ታሪክ እንዲማሩ እየተደረጉ መሆኑን በመግለጽ በዚህ ስብሰባ ያልተገኘ አስተማሪ በ2007 ዓ.ም በመምህርነት ስራ ላይ ተሰማርቶ እንደማይሰራ እንደተነገራቸውም ለማወቅ ተችሏል።
     ስብሰባው በወረዳው ፅህፈት ቤት ሓላፊ በሆነው አቶ ጊዱማ ታደሰ በተባለ ካድሬ የተመራ ሲሆን ይህ ካድሬ በስብሰባው ላይ ኦህዴድ ኢህአዴግ ልማታዊና ዴሞክራሲያዊ መንግስት ስለሆነ በመጭው ምርጫ ድርጅታችንን መምርጥና የበኩላችንን ማበርከት ይገባናል አለበለዚያ ግን ሃገራችን ለከፍተኛ ጥፋት ትዳረጋለች እያለ ቅስቀሳ እያደረገ የሰነበተ ሲሆን አስተማሪዎቹ ግን በአንፃሩ ያላሰበውን ጥያቄ አንስተው ስላስጨነቁት የሻሂ ሰዓት ደርሷል በማለት ከስብሰባው ሊወጣ እንደቻለ ለማወቅ ትችሏል።
ከተነሱት ጥያቄውች የተወሰኑትን ለመጥቀስ።-
·         የሃገራችን ዜጎች ህጋዊ ባልሆነ መንገድ  ለምን ይታሰራሉ?
·         መንግስት ለምንድነው በየአመቱ አዳዲስ ፍልስፍና እያመጣ ህሊናችንን እያሳመመን ያለው?
·         ድኻ ወገናችን ፆሙን እያደረ የመንግስት ባለስልጣናት ግን ለምንድነው በተለያዩ የሃገራችን ከተሞች ቪላዎችንና ፎቆችን እየሰራችሁ ያላችሁ?
·         የአባይ ግድብ በአምስት አመት ውስጥ ይጨረሳል ስትሉ ከርማችሁ ለምንድነው አሁን ቃላችሁን አጥፋችሁ በሰባት አመት ነው የሚጨረስ  እያላችሁ ወሬአችሁን የምትነዙ
የሚሉና ሌሎችም ጥያቄዎች መነሳታቸውና ለነዚህ ጥያቄዎች ተገቢው መልስ ሳይሰጥባቸው ስብሰባው መስከረም 15/2007 ዓ.ም እንደተጠቃለለ ምንጮቻችን ከስፍራው በላኩልን መረጃ ለማወቅ ተችለዋል።