Sunday, August 30, 2015

በአዊ ዞን ጃዊ ወረዳ የሚገኙ ንፁሃን ወጣቶች በትጥቅ ትግል ከሚንቀሳቀሱ ድርጅቶች ጋር ግንኙነት አላችሁ በሚል ሰንካላ ምክንያት እየታሰሩ መሆናቸውን ከስፍራው የደረሰን መረጃ አመለከተ።



     የደርሰን መረጃ እንዳመለከተው በአዊ ዞን ጃዊ ወረዳ ወርቅ ሜዳ ፈንደቃና ደቅ ዘረገነት በተባሉ ከተሞች የሚኖሩ ንፁሃን ዜጎችን በትጥቅ ትግል ከሚንቀሳቀሱት  ከአርበኞች ግንቦት 7ና ከትህዴን ጋር ውስጣዊ ግንኙነት አላችሁ በሚል የሃሰት ውንጀላ ከ13 በላይ ወጣቶች በነሃሴ ወር መጀመሪያ አካባቢ ተይዘው እንደተወሰዱ እስካሁን አድራሻቸው እንደማይታወቅ የገለፀው መረጃው ሰላማዊ የፖለቲካ ትግል የሚያካሂዱ ድርጅቶችን ስትደግፉ ቆይታችሁ አሁንም የምርጫው ውጤት አልሳካላችሁ ሲል የትጥቅ ትግል ከሚያደርጉ ድርጅቶች ጋር ግንኙነት አላችሁ በማለት እያሰሯቸው እንደሚገኙ ተገለፀ።
    ይህ በእንዲህ እንዳለም በወረዳው ከዚህ በፊት በተመሳሳይ የሃሰት ውንጀላ ታስረው ከ25 በላይ ወጣቶች ለሁለት አመታት ያህል ሲሰቃዩ ከቆዩ በኋላ የትራፊክ ፖሊስ ሳጂን አበጀ የተባለውን ጨምሮ ሶስት ወጣቶችን ፍርድ ቤት ለክስ የሚያበቃ ወንጀል የላቸውም ብሎ የለቀቃቸው ሲሆን ከሚሰሩበት መስሪያ ቤት ተባርረው በየትኛውም የመንግስት መስሪያ ቤት እንዳይሰሩ ተከልክለው እንደሚገኙ የተገኘው መረጃ ጨምሮ አስረድቷል።