Wednesday, February 8, 2017

በጥሩ አንደበት ያሸበረቀ፥ ጥሩ ያልሆነ የወያኔ ኢህአዴግ ተግባር!!



አንድ መንግስታዊ ስልጣን የተረከበ ፓርቲ ወይም ግንባር እንደሥነ-ምግባር፣ የሚመራውን ህዝብ አገልጋይ ሆኖ ሲታይና በገባው ቃልና ኃላፊነት መሠረት ህዝብ የሚፈልገውን ለመተግበር ተስፋ የሚደረግበት አካል ነው።  

ይህ ግን በአገራችን ኢትዮጵያ ትርጉሙን ከማወቅ የዘለለ፣ የዚህ መልካም ተግባር ተቋዳሽ እንድንሆን ያልታደልነው ዕድል ሆኖ ቆይቷል። ያለፈው እንዳለ ሆኖ የኢትዮጵያ ህዝብ ያለ ስርዓት ለውጥ ለ25 ዓመታት ሲጓዝ፣ የገዥው ኢህአዴግ ስርዓት ውጤታማ ተግባራዊ እንቅስቃሴ ኖሮት እየደገፈውና እየተደሰተ ሳይሆን፣ ዓመታት በጨመረ ቁጥር ስቃዩና መከራው እየጨመረ ነው የመጣው።  
ተጨባጭ ማሣያው ደግሞ ህዝባችን እንደዚህ መሆኑ፣ በእነዚህ ባሳለፋቸው ዓመታት ውስጥ ያለው የህዝባችን ነባራዊ ህይወትና በላዩ ላይ ገኖ የሚታየውን ስቃይና መከራ በጥልቀት መገንዘብ አስፈላጊ ነው። እዚህ ላይ የሚገርመው ግን፣ ለዚህ በዓይነቱ የሰፋና በኢትዮጵያ ታሪክ ተወዳዳሪ የሌለው ጭቆና፣ እንዲሁም ከዚህ ጋር አብሮ ያደገው በህዝባችን መካከል ተፈጥሮ ያለውን የአንድነት መሻከር፣ ስርዓቱ በጥሩ ዓይን ተመልክቶ የለሰለሱ ጣፋጭ ቃላትን በአንደበቱ እየተናገረ የህንን ገፅታ በግልባጭ ምስል አድርጎ ሊያሳየን መሞከሩ ነው።  

ይህ ማታለል ደግሞ ቀጣይ ምሬት ከኢህአዴግ የስልጣን ጉዞ ጋር እኩል እየቀጠለ ይገኛል። ይህ ግን እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል ካልሆነ በስተቀር እንዳለው ይቀጥላል ማለት ዘበት ነው።ሊቀጥል እንደማይችልም የህዝባችን አሁን ያለው እንቅስቃሴ ምን እየሆነ እንዳለ የሚመሰክረው ሐቅ ነው።ካልሆነ ግን የወያኔ ኢህአዴግ የሌለን መኳኳል ያለፈው እንዳለ ሆኖ፣ አሁንም የአለምን ህዝብ ቀልብ ስቦ ላለው የህዝባችንና የአገራችን አደጋ ትልቅ ትኩረት ሰጥቶ ህዝብ የሚጠይቃቸውን ጥያቄዎች ተገቢ ምላሽ ከመስጠት ይልቅ፣ እርስበርሳቸው በሚጋጩ ምክንያታዊ ባልሆኑ ሰበቦች ሲደረድር፥ ማለት በአንድ በኩል የውጭ ኃይሎች ጣልቃ ገብነት በሌላ በኩል ደግሞ የትኛው ጥሩ አካሉ መሆኑን የማያውቀው እንደ ሁለተኛ አካሉ አድርጎ የሚጠቅሰው የክስተቱ ዋና መነሻ አድርጎ ሲፎክር እየሰማን ነው።  

ይህ ግን በትክክለኛ አይን ታይቶ ችግሩ በእነዚህ አካሎች መሆኑ ታውቆ ሳይሆን፣ ለዚህ በአይነቱ የከፋ ጫና ፈንቅሎ ከእነዚህ ሃላፊነታቸውን የረሱ የስርዓቱ አገልጋዮች አቅም በላይ በመሆን ስርዓት ለመቀየር እየታገለ ያለውን ባለህሊና ህዝብ ተመልሶ የሚጨፈልቅበት መንገድ የተመረጠ ማሳኪያ መሆኑ ነው። የሚያሳዝነው ግን እንግዳ ተግባር የሆነ የስርዓቱ ማጣፈጫ አሁንም አጋጥሞ ያለው ቀውስ ተሃድሶ በሚል አዲስ አርዕስት ለውጥ ተደርጎ እያንበደበደው መሆኑ ነው።

የሚገርመው ደግሞ ህዝባችን ባልመረጠው አርዕስት የሚፈልገውን መልስ ለማግኘት ባይጠብቅም፣ በዚህ ሂደት የተከፈተ በየደረጃው በተካሄደው መድረክ ግን ህዝባችን ለሚያነሳቸው ችግሮች መቋጫ አግኝተው፣ የዚህ ችግር ባለቤት ህጋዊ ተጠያቂነት አለማግኘቱ ሳይበቃ፣ በስርዓቱ የስሙልኝ ጩኸት፣ የሰራነው የሚደክም፣ የሚል አይነት ደስ አይበላቸው ምላሽ እየታለፈ ነው ያለው። ይሁን እንጂ ይህ መሆን አለበት ወይ? የሚለው ሌላ ጉዳይ ሆኖ፣ አመል እስከመግነዝ እንደሚባለው ግን፣ የኢህአዴግ ስርዓት እስካለ ጥሩ ምላስ ልንሰማ ካልሆነ በስተቀር፣ ጥሩ ተግባር ማየት ግን ዘበት ነው።

No comments:

Post a Comment