Thursday, January 3, 2013

የዓዲ-ሃገራይ ከተማ ኗሪዎች መንግስት ከፍተኛ ግብር በመጫን እየበዘበዘን ነው ፥ የናነተ እዚህ ድረስ መምጣት ለህዝቡ አስባችሁ ሳይሆን ለዘረፋ ነው ሲሉ የከተማዋን ህዝብ ለማነጋገር ከክልሉ መንግስት ለተላከ ቡድን በስርዓቱ ላይ ያላቸውን ቅሬታ በምሬት ገለጹ።

በሰሜናዊ ምዕራብ ትግራይ በታሕታይ አድያቦ ወረዳ የዓዲ-ሃገራይ ከተማ ኗሪዎች መንግስት የጫነባቸውን ከፍተኛ ግብር በመቃወማቸው ምክንያት ኗሪውን ለማረጋጋት ሲባል ታህሳስ 21,2005 ዓ/ም ከክልል የተላኩ ባለስልጣናት ህዝቡን በመሰብሰብ ሊያስረዱ ቢሞክሩም እንዳልተሳካላቸው የደረሰን ዘገባ ያመለክታል።
ላልፉት 21 ዓመታት በክልሉ መንግስት የተረሳው ታጋዩ የዓዲ-ሃገራይ ህዝብ አሁን በአከባቢው እየተጠናከረ የመጣውን የህዝብ ተቃውሞ በማየት የክልሉ መንግስት ከንጹህ የመጠጥ ውሃ ጀምሮ መሟላት የሚገባቸውን ሌሎች የመሰረተ ልማት እንዲሟሉ እንሰራለን በማለት የማይተገብሩት ቃል በመግባት ህዝቡን ለማግባባት ቢሞክሩም ህዝቡ ከናንተ የምንጠብቀው አወንታዊ ነገር የለም በማለት ፊት እንደነሳቸው ቷውቋል።
በስርዓቱ ከፉኛ የተማረረው የከተማው ኗሪ ህዝብ እናንተ ህዝብ ስትሉ ህዝብን ለመበዝበዝ እንጂ ስለ ህዝብ አስባችሁ አይደለም ፥ ባሳለፍናቸው 21 ዓመታት እስኪበቃን አየናችሁ ፥ ተዛዝበናል ። ችግራችን ለመፍታት ከትህዴን ጎን ተሰልፈን ለመታገል አቋም እንወስዳለን ሲሉ ከክልል ለተላኩት ልኡካን ገልጸውላቸዋል።
ከክልል የተላከው ቡድንም የኣዲ ሃገራይ ህዝብ ከትህዴን ጋር ተሰልፎ ለመታገል መቁረጡን ለአለቆቻችን እናስረዳለን በማለት በህዝቡ ላይ ያለውን ንቀት አንጸባርቋል።
ይህ በእንዲህ እያለ መንግስት በህዝቡ ላይ የጣለውን ከፍተኛ ግብር በመቃወም በዓድዋ ከተማ የተነሳውን የህዝብ ተቃውሞ ለማረጋጋት ጠ/ሚኒስትር ሃ/ማሪያም ደሳለኝ ዓድዋ ድረስ ሄዶ እንደነበረ ለማወቅ ተችለዋል።