Monday, April 29, 2013

በትግራይ ክልል የፖሊስ ሃይል ውስጥ የተፈጠረውን መከፋፈልና እርስ በርስ ያለመተማመን ሁኔታ ለመገምገም በመቐለ ከተማ ውስጥ በክልል ደረጃ የፖሊስ ግምገማ መጀመሩን ከቦታው የደረሰን ዘገባ ያመለክታል፣



በደረሰን ዘገባ መሰረት የኢህአዴግ ስርዓት በሚከተለው ብልሹ አስተዳደር ምክንያት በክልሉ የፖሊስ ሃይል ውስጣዊ ዴሞክራሲያዊ አሰራር ጠፍቶ ለዓመታት ስር ሰዶ የቆየ መከፋፈል በአሁኑ ግዜ ጫፍ ደርሶ የስርዓቱን ህልውናን መፈታተን በመጀመሩ በክልል ደረጃ ከወረዳ ጀምሮ እስከ የክልሉ ከፍተኛ የፖሊስ አዛዦች የተገኙበት ግምገማ ከሚያዝያ 21,2005 ዓ/ም ጀምሮ በመቐለ ከተማ ለማካሄድ ተገዷል፣
በክልሉ የፖሊስ ሃይል መካከል የተፈጠረው መከፋፈል ዓመታት ያስቆጠረና በተገልጋዩ ህዝብረተሰብም ከባድ ጉዳት ሲያደርስ የቆየ ሲሆን ህዝቡ ከክልሉ የፖሊስ ሃይል ማግኘት የሚገባውን አገልግሎት በአግባቡ ማግኘት እንዲችል የማስተካከያ እርምጃ እንዲወሰድ በተደጋጋሚ ለሚመለከተው አካል ያቀረበውን ጥያቄ ትኩረት ሳይደረግበት ቆይቷል፣ አዲስ ነገር የተፈጠረ ይመስል አሁን ደርሶ ግምገማ ማድረግ ህብረተሰቡን በቅንነት ለማገልገል ታስቦ ሳይሆን በህዝብ የተተፋውን ጸረ-ዴሞክራሲ ስርዓት ጠጋግኖ ለማሰንበት የሚደረግ ራስን የማዳን ሙከራ ነው ሲሉ የውስጥ አዋቂዎች ይናገራሉ፣
በሽረ እንዳስላሰ ከተማ በፖሊስ አባላት መካከል በተፈጠረው አለመግባባት በርካታ የፖሊስ አባላት መታሰራቸውን ከዚህ ቀደም መዘገባችን የሚታወቅ ሆኖ እንደዚሁም በራያ ዓዘቦ ፤በመኾኒ ፤ አላማጣ ፤ ሽረና ሌሎች አከባቢዎች በክልሉ መንግስት የተወሰደው የኗሪው ህዝብ መኖሪያ ቤት የማፍረስ እርምጃ አንዳንድ የፖሊስ አባላት መቃወማቸው የሚታወስ ነው፣