Sunday, June 18, 2017

በአገራችን የለውጥ ኃይሎች ላይ የሚያጋጥሙ ተግዳሮቶች



    የአገራችን ህዝቦች በላያቸው ላይ የተጫነውን የጥፋት በደል ለመበጠስ ሲሉ የተለያዩ ገፅታዎች ያሏቸው የትግል አማራጮችን በመያዝ ለ26 ዓመታት ሙሉ ያለእረፍት ከገዥው ስርዓት ተቃራኒ ሲንቀሳቀሱ መቆየታቸውና መሆናቸው የሚታወቅ ነው።
    ስርዓቱ ደግሞ አስቆጥሯቸው ባለው 26 ዓመታት ውስጥ ከጊዜ ወደ ጊዜ እራሱ አርቅቆ ያፀደቃቸውን የዜጎች ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች በመጣስ፤በማገድና ለስልጣኑ ከለላ የሚሆኑትን ዘዴዎች በመከተል ወደ ለየለት ፀረ ህዝብ እና ፀረ ህገመንግስት ተግባሮች ተሰማርቶ የዴሞክራሲ ግንባታንና የሃገርን እድገት አጨናግፎ በግላዊ ኑሮውና ሙስና ተዘፍቆ ሊወጣው ወደማይችለው ቅልውላው ገብቶ እንዳለ ገሃድ ሐቅ ነው።
    እነዚህ በየወቅቱ በህዝብ ላይ ሲያደርሳቸው የቆዩና ያሉ ዘርፈ ብዙ በደሎች ደግሞ መግቻ እንዲያደርግላቸው ከህዝብ በተለይ ደግሞ ገስጋሽ ከሆኑ የለውጥ ሃይሎች በሕገመንግስቱ በሰፈረው መብት ተጠቅመው የስርዓቱን ተግባሮች በግልፅ ያጋለጡ፤ሐሳባቸውን በነፃ የሚገልጡ እና የተቃዎሙ ወገኖችን ዘላቂ የሆነ መፍትሄ ከመፈለግ ይልቅ አንገታቸውን እንዲደፉና ከህዝብ እንዲነጠሉ የሚያስችሉ መንገዶችን በማጠናከር ከዚህ ባለፈም አግቶ ህልውናቸውን  በማጥፋት፤በመግደል ብሎም ወደ ወህኒ ቤት በማጎር ያልፈፀሙትን ወንጀል እመኑ እየተባሉ ለስቃይ እየተዳረጉ የመጡና ያሉ ዜጎች በተለይ ደግሞ ምሁራን፤የተቃዋሚዎች አባላትና አመራሮች በጣም ብዙዎች ናቸው።
    ይህ ፀረ ህዝብ ስርዓት በለውጥ ኃይሎች ላይ እያደረጋቸው ያለው አፈናና እስራት ሁሉንም የኢትዮጵያ ህዝብ እያሰረውና እያነቀው መሆኑ ግን አልተረዳውም። ምክንያቱም ህዝብ የሚያስብ ህሊና፤ የሚያይ ዓይንና ሰሚ ጆሮ ስላለው፥ አማራጭ ሃሳብና ፖሊሲ ይዞ የሚንቀሳቀሰውን ሃይል ደግሞ ራሱ ህዝቡ ነው ሊያርቀውና ሊደግፈው የሚገባ።
    ይሁን እንጂ የፖለቲካ ወይም የዴሞክራሲ ተቋማትና ፖለቲከኞች መስፋፋትና መጠናከር ባለቤት መሆኑን ረስቶ በህዝብ ዘንድ ጥሩ ተቀባይነትና ድጋፍ ያላቸውን ምሁራንና ፖለቲከኞች ብሎም ተራማጅ ድርጅቶችን ከማበረታታትና ከማጎልበት ይልቅ በተለያዩ መንገዶች እያደረገ ሲያዳክማቸው፤ ሲበትናቸውና ሲያስራቸው እንዲሁም በላያቸው ላይ በገንዘብ በተገዙ የፀጥታና የደህንነት አካላት በኩል አድርጎ ጉዳት ሲያደርስባቸው ነው እየታየ ያለው።
    በመሆኑም በየጊዜው ስለፍትህ፤ ዴሞክራሲና የህግ የበላይነትን ለማንገስ ሲሉ የመሰላቸውን ሃሳብ ከስርዓቱ በሚቃረን በመፃፋቸው፤በመቃዎማቸው፤ ወደ አደባባይ ወጥተው ሰላማዊ ሰልፍ በማድረጋቸው ብቻ የስርዓቱ ቅጥረኛ የፀጥታ ሃይሎች የጥይት እራት እየሆኑ የሞቱ ከባድና ቀላል ጉዳት የደረሰባቸውና የታሰሩ ወገኖች እጅግ ብዙዎች ናቸው።
    በዚህ ላይ ሁሉንም ባንዘረዝርም እንኳ በምሳሌነት ማንሳት ግን ይቻላል። ማለትም በቅርብ ዓመታት ተመስርቶ በህዝብ ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነትና ድጋፍ የነበረው ሰማያዊ ፓርቲ በምን ሁኔታ ላይ አለ? የኦሮሞ ኮንግረስ በመባል የሚጠራው ፓርቲ አመራሩና አባላቱ ምን አይነት እጣ ደረሳቸው እንዲሁም የዓረና ትግራይ ተቃዋሚ ፓርቲ በአባላቱና በአመራሩ ላይ በህወሃት ካድሬዎችም ይሁን በደህንነቶች ምን አይነት በደልና አፈና እየደረሰበት እንዳለ በዚህ ሳምንት በድርጅቱ ሊቀ መንበር አብርሃ ደስታ ላይ የደረሰው ጥቃት በቂ ምስክር ነው።
    ስለዚህ የወያኔ ኢህአዴግ ፀረ ህዝብ ቡድን የለውጥ ኃይሎች በሆኑ ግለሰቦችና ድርጅቶች ላይ እየደረሰ ያለው ጥቃት በሚሊዮኖች ህዝቦች ላይ እየፈፀመ እንዳለ በመረዳት ሁሉም ለውጥ ፈላጊ አይሆንም ሊለው ይገባል እንላለን።

No comments:

Post a Comment