Sunday, June 4, 2017

ህዝብን እያስለቀሱ የሚረጋገጥ ልማት የለም!!



    ይህ በስልጣን ላይ በመሳሪያና ባሰማራቸው የፀጥታ ሃይሎቹን ከለላ አድርጎ ወደ ማይቀረው ውድቀቱና ውድመቱ እያመራ ያለው የወያኔ ኢህአዴግ ቡድን፣ አስቆጥሯቸው ባለው 26 ዓመታት ውስጥ እወክለዋለሁ እመራዋለሁ በሚለው ህዝብ ላይ ይህ ነው ተብሎ ለመገመት የሚያስቸግሩ በደሎችንና ግፎችን እያወረደ፣እያስለቀሰ ከድህነትና ከመንከራተት የማያድን ለራሱ ብቻ ልማት ብሎ በመሰየም በመጓዝ ላይ ይገኛል።
    ይህ በየወቅቱ በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ የሚያደርሳቸው በደሎች ሁሉንም ዘርዝሮ ለመጨረስ ባይቻልም፦ከብዙዎቹ ግን አንዱን እንደምሳሌ ለማንሳት መርጠናል። እሱም ለመሰረተ ልማትና ለከተሞች መስፋፋት በሚል ስም ግንባታውን ለማጠናቀቅ እየተባለ በመሬት አጠቃቀም ላይ እየታየ ያለውን የኢህአዴግ ሙስኛነትና አውዳሚ አካሄድ የተመለከተ ነው።
    ይህንን የአርሶ አደሮች መሬት በእርሻና ሌሎችም ኑሯቸውን እየመሩ ባህላዊ ክብሮችንና ልምዶችን ለረጅም ዓመታት እየተወራረሱ በቆዩ ወገኖች ላይ ተመጣጣኝ ካሳ ሳያገኙ መሬታቸውን ቀምቶ በመወርወር ለተለያዩ ችግሮች እየተጋለጡና ለድህነት፤ለሥነ-ልቦና ጥቃት እና ስቃይ እያደረሰባቸው መጧል። አሁንም እያደረሰባቸው ይገኛል።
    በከተሞች የሚኖረውን ህዝብ ደግሞ ለተቋሞችና ለግል ባለሃብቶች እየተባለ የድሆችን ቤት አፍርሶ እነዚህን ደሃ ቤተሰቦች ለፀሃይና ለብርድ አጋልጦ፣ አፋጦ በመያዝ ማግኘት የሚገባቸውን ጥቅሞች እያጡ ጊዜ የሚቆጥሩ ወገኖች በጣም ብዙዎች ናቸው።
     ለልማትና ለተቋሞች እየተባለ በየአካባቢው የሚገኝ ለም መሬት እየተመረጠ ግንባታው ሊጀመር ነው ተብሎ የመሰረት ድንጋይ ከተቀመጠ በኋላ መና ሆኖ የሚቀርና ግንባታው ተጀምሮ በሙስናና በማጭበርበር አገልግሎት ሳይሰጥ በሁሉም አካባቢ አመታት እያስቆጠረ ያለውን ለመገመት የሚይስቸግር አይደለም።
    ለዚህ መዝጊያ እያንኳኳ ለአደጋና ለድህነት እያጋለጠ ያለው የወያኔ ተግባራት መቋጫ እንዲያገኝ ምንም እንኳ በህዝቡ ቅሬታም ይሁን አቤቱታ የሚቀርብ ቢሆንም የህዝብን ስሞታና ስቃይ ሰምቶ መፍትሄ የሚሰጥ አካል ሊገኝ ግን አልቻለም።
    የድሆችን መሬት በሃይል ቀምቶ የሚለማ ልማት ውድመት እንጂ እድገትን አያመጣም። ምክንያቱም ህዝብን አስተዳድራለሁ የሚል አካል አስቀድሞ ባለቤት ከሆነው ህዝብ ጋር የጋራ መግባባትና ግልፅነት የተሞላበት አሰራር በመከተል ጥቅሞቹንና ችግሮቹን በመረዳት የተለያዩ መሰረተ ልማቶችን ሊያቀላጥፍ ይችላል።
    ህዝብን ሳታሳምን በማን አለብኝነት የሚካሄድ ክዋኔ ግን ውድመት እንደሚያስከትል ባለፉት ቅርብ ወራት ግንባታቸው ዓመታት የጨረሱ ተቋማት በደቂቆች ሲወድሙ ታይተዋል። ይህ ፍፃሜ ደግሞ ህሊና ላለው ሰው ትልቅ ትምህርት ትቶ አልፏል። ስለዚህ አውዳሚ ተግባራት እየፈፀሙ ያሉት ኢህአዴጋውያን ከዚህ ሊማሩ ይገባቸው ነበር። ሆኖም ግን ከህዝብ ተነጥሎ ህዝብን በሚቃረን መንገድ እየተጓዘና እየደለቀ በመሄድ ላይ ያለ ቡድን ስለሆነ የህዝብን ጥቅም አሽቀንጥሮ ግላዊ እርምጃውን በማከናወን ላይ ነው እየታየ ያለው።
    ለምሳሌ በየጊዜው በከተሞች ቤቶቻቸው በዶዘሮች እየፈረሱባቸው ዓይኖቻቸው በእንባ እየታጠቡ ለሐሩር፤ለብርድና ለእንግልት የተዳረጉ ዜጎች ስንቶች ናቸው? ይመርም ይክፋ በእርሻ ኑሯቸውን ሲመሩባት የቆዩ መሬታቸውን ያለ በቂ ካሳና ያለመጠለያ እየተቀሙ ለተለያዩ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች እየተጋለጡ የመጡና ያሉ ወገኖችስ ምን ያክል ናቸው ከተባለ ቤት ይቁጠራቸው ነው።
    አሁንም የዚህ ድርጊት ተጎጂ የሆኑ የያዩ ብረታ ብረት ኢንጅነሪንግ ኮርፖሬሽን ፋብሪካ መስሪያ ተብሎ ከመሬታቸው የተፈናቀሉ ወገኖች የካሳ ክፍያ አላገኘንም፣ ተገቢ ክፍያ ለሚገባው ሰው ከሚያገኝ ይልቅ በአጭበርባሪዎችና ሙሰኛ አመራሮች የተነሳ ለተለያዩ ችግሮች ተጋልጠው እንዳሉ በመግለፅ ላይ ይገኛሉ። ስለዚህ ዜጎችን እያስለቀሱ የሚካሄድ ልማት ሊቆም ይገባል። በማንኛውም ዓይነት ምክንያት ከመሬቱ ለተነሳ ዜጋ ደግሞ ቅድመ መግባባትና ስምምነት በማድረግ የሚገባውን ካሳና መቆቋሚያ ሊያገኝ ይገባዋል።

1 comment: