Wednesday, April 27, 2016

የመልካም አስተዳደር ምሬትና መፍትሔ አልባነት!!



ገዥው የኢህአዴግ ስርዓት ኢትዮጵያን ማስተዳደር ከጀመረበት ጊዜ ጀምሮ፣ ህዝቦችን በተጨቋኝነት ቀምበር ስር በመጥመድ፣ አገራችን የስልጣኔ በራፍን እንዳትረግጥ የኋላቀሮች ኋላቀር አድርጓታል።
 ብዙ መስራትና አገርን መገንባት የሚችሉ ምሁራንና ወጣቶችን ከመሬት ገፅ አጥፍቷቸዋል። አብረው በሰላምና በፍቅር የኖሩ የነበሩትን የኢትዮጵያ ብሄር ብሄረሰቦች በመከፋፈልና በመካከላቸው ገብቶ በሰይጣናዊ ድርጊቱ እሳት በመለኮስ፣ እርስ በርሳቸው እያነካከሰ ይሄው እስካሁን ድረስ የስልጣን እድሜውን እያራዘመ ይገኛል።
    ስርዓቱ ለጥፋት የቆመ ነውና ሙስና፤ ጉቦኝነት፤ አድሎአዊነት፤ ዘረኝነትና ኪራይ ሰብሳቢነት ከደሙ ጋር የተወሃሃዱ፣ የአገርን ሃብት ሲበዘብዝበት የቆየ የውድመት ቀመሮቹ ናቸው። ስርዓቱን ለመቃወም የሚያቆጠቁጡ እምቡጥ የፖለቲካ ተቃዋሚ ድርጅቶችን መጨፍለቅ ደግሞ፣ ዋነኛ የዕድሜው ማራዘምያ  ስንቁ ናቸው።
 ይሄንን የኢህአዴግ ድብቅ አጀንዳና አገርን የመከፋፈል ተግባር በትኩረት የተመለከተው የኢትዮጵያ ህዝብ፣ በአሁኑ ጊዜ በሁሉም አካባቢ የተቃውሞ ድምፁን በግልም ሆነ በጋራ እያሰማ ይገኛል። የአንገዛም ባይነትና አመፅ የተቀላቀለባቸው የጋራ ህዝብ ትዕይንቶች በሁሉም አካባቢ ተቀጣጥለዋል። የትምህርት ተቋማት ከመለስተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች እስከ ከፍተኛ ዩኒቨርስቲዎች ከገጠር እስከ ማዕከል ርዕሰ ከተማ፣ የተማሪዎች ዓመፅ በአምባገነኖች ላይ እንደመብረቅ ወርዶባቸዋል፣ የታክሲ ሹፌሮች የስራ ማቆም አድማም ለፋሽስቱ ገዥው የኢህኣአዴግ ቡድን ዱብዳ ሆኖበታል።
ለዘመናት ታፍኖ የኖረው ህዝብ ዛሬ ግን ድር ቢያብር በማለት ለየብቻ በጨለማ ከመረሸን በአንድነት አምባገነኖችን ፊት ለፊት መተናነቅ የመጨረሻ ምርጫው በማድረግ ከጫፍ እስከ ጫፍ መስዋዕት እየከፈለ ይገኛል።
የህዝቡ አመፅ ያስደነገጠው ስርዓቱ፣ ዳግም በስልጣን የሚቀጥልበትን ቀመሩን ከማሰላሰል አልዳነም። የህዝቡን ወቅታዊ ቀልብ የሚስብበትን መላ መዘየድና ተቃዋሚዎችን የሚያቀዘቅዝበትን ዘዴ  በመፍጠር፣ አስጊ ያላቸውን ህዝባውያን ግለሰቦችና ድርጅቶች ላይ አረመኔ እርምጃ መውሰድ ብቸኛ መፍትሔው እያደረገ ይገኛል።
እናም የመልካም አስተዳደር ንቅናቄ በሚል የማደናገሪያ ስልት ህዝቡ ውስጥ በመስረግ የሴራ መርዙን እየረጨ ይገኛል። ኢህአዴጋውያን እንዳሰቡት ሳይሆን፣ ህዝቡ በተቃራኒው “እናንተ ታሻሽላላችሁ ብለን የምንጠብቀው ነገር የለምና ከስልጣናችሁ ውረዱልን”   ሲል የመጨረሻ ምሬቱን፣ በኢህአዴግ ላይ ያለውን ጥላቻ በገሃድ በማስተጋባት ላይ ቢገኝም፣ ከታችኛው እስከ ፌደራሉ የመንግስት ባለስልጣናት ግን  ጉድለቱ የእኛ ነው እያሉ ቢያስተማስሉም፣ አሁንም የፈጠሩትና የለወጡት መፍትሔ የለም። እንዲያውም ለራሳቸው ስጋት የሆነባቸውን ሰው፣ ሙሰኛ ብለው ከስልጣን ያባርሩታል፣ ገና እንዲበላ የተፈለገውን ደግሞ ከወረዳ ወደ ወረዳ ከዞን ወደ ዞን ቢቀይሩት ለህዝብ እና ለአገር የሚበጅ ምንም መፍትሔ ሊያመጣ ስለማይችል፣ በአገራችን ላይ የህዝቡን የመልካም አስተዳደር ምሬት መፍትሔ ሊገኝበት አልቻለም።

No comments:

Post a Comment