Friday, April 27, 2018

በኮማንድ ፖስቱ የተያዙ ተጠርጣሪዎችን ፈተዋል የተባለ ዳኛ በኮማንድ ፖስቱ ለአራት ቀናት መታሰሩ ተገለጠ።



በኦሮሚያ ክልል በምሥራቅ ሐረርጌ ዞን በደኖ ወረዳ የመጀመርያ ፍርድ ቤት ዳኛ የሆኑት አቶ አብነት ታደሰ ተጠርጣሪዎች ናቸው የተባሉ ሦስት ግለሰቦችን በነፃ በማሰናበታቸው፣ ዓርብ ሚያዝያ 12 ቀን 2010 ዓ.ም. በወረዳው የኮማንድ ፖስት ዕዝ እንዲቀርቡ ተጠርተው በዚያው መታሰራቸውን ዳኛው አቶ አብነት ታደሰ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
ከዳኛው በተጨማሪም ተጠርጣሪዎቹን ፍርድ ቤት ይዘው ያቀረቡ አንድ ዓቃቤ ሕግም፣ ለአንድ ቀን ከታሰሩ በኋላ መፈታታቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡
ዓርብ ሚያዝያ 12 ቀን 2010 ዓ.ም. ከቀትር በኋላ በወረዳው የኮማንድ ፖስት ዕዝ ጽሕፈት ቤት እንደሚፈለጉ ጥሪ እንደደረሳቸው የገለጹት አቶ አብነት፣ ‹‹የወረዳው ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት ውክልና ሰጥተውኝ ለፕሬዚዳንትነትም እያገለገልኩ በመሆኑ፣ አስተዳደራዊ ጉዳዮችን በተመለከተ ፈልገውኝ ይሆናል ብዬ ብሄድም ጉዳዩ ተጠርጣሪዎቹን በተመለከተ ሆኖ በቁጥጥር ሥር አውለውኛል፤›› ብለዋል፡፡
ሰኞ ሚያዝያ 15 ቀን 2010 ዓ.ም ደግሞ ወደ ምሥራቅ ሐረርጌ ዞን ፖሊስ መምርያ ይዘዋቸው እንደሄዱ፣ በወቅቱም የመምርያው ፖሊስ አዛዥ ደንግጠው፣ ‹‹ዳኛ እንዴት ሊታሰር ቻለ?›› ብለው እንደጠየቁ አቶ አብነት ተናግረዋል፡፡
አንድ የመከላከያ ሠራዊት ሻምበል፣ የወረዳው ፖሊስ አዛዥና የወረዳው የፀጥታና ደኅንነት ጉዳዮች ኃላፊ እንደጠበቁዋቸው ገልጸዋል፡፡
በኋላም የተፈጠረውን ነገር ተረጋግተው ለፀጥታ ኃላፊዎች እንዳስረዷቸው የሚናገሩት አቶ አብነት፣ ‹‹በመጨረሻም ይቅርታ ጠይቀውኝ ሰኞ ዕለት 15 /2010 ዓ/ም ከቀትር በኋላ ተፈትቻለሁ፤››ሲሉ የገጠማቸውን እንግልት ለሪፖርተር መግለፃቸው ለማወቅ ተችለዋል፡፡

No comments:

Post a Comment