Monday, July 21, 2014

በአዊ ዞን የሚገኙ አርሶ አደሮች የጤፍ ምርጥ ዘር መግዛትና በመስመር መዝራት በመቃወማቸው ብቻ በገንዘብና በእስር እየተቀጡ በመሆናቸው በስርዓቱ ላይ ምሬታቸውን እያሰሙ እንደሚገኙ ምንጮቻችን ከቦታው ገለጹ።



እነዚህ በአማራ ክልል አዊ ዞን በማንጃና በአንከሻ ወረዳዎች የሚገኙ አርሶ አደር ዜጎቻችን በአካባቢው አስተዳዳሪዎች የጤፍ ምርጥ ዘር ገዝተው በመስመር እንዲዘሩ መመሪያ ያወርዱባቸው ሲሆን አርሶ አደሮቹ በበኩላቸው የጤፍ ምርጥ ዘር ዋጋ ከመወደዱም በላይ ጤፍ በመስመር መዝራት አድካሚና አስልቺ እንዲሁም ከቁጠባችን ጋር የማይጣጣም ነው በማለት የወረደውን መመሪያ እየተቃዎሙት እንዳሉ ታወቀ።
  ጤፍን በመበተን እንጂ በመስመር አንዘራም በማለት ለወረደው መመሪያ የተቃዎሙ አርሶ አደሮች በስርዓቱ ታጣቂዎች 35 የሚደርሱ ገበሬዎች ለአንድ ሳምንት ታስረው ከቆዩ በኋላ ምንም አይነት በደል ሳይፈፅሙ  ለእያንዳንዳቸው አንድ መቶ ብር ተቀጠው እንደተለቀቁና ለከፈሉት ብርም ደረሰኝ እንዳልተሰጣቸው የተገኘው መረጃ አስታውቋል።
  በስልጣን ላይ ያለው መንግስት ለነዚህ ገበሬዎች አስተምሮና ተገቢውን ምክር ሰጥቶ በሃገራቸው ልማት እንዲሳተፉ ከሚያደርግ ይልቅ ያወረድነውን መመሪያ አልተቀበሉም እያለ ገበሬዎችን በአዝመራ ወቅት ወደ እስር ቤት እየወሰደ ማሰሩ ወጤት አይኖረውም ብለው እያሉ የአካባቢው ህብረተሰብ በስፋት እየተነጋገሩበት እንደሚገኙ  ምንጮቻችን በላኩት መረጃ ለማወቅ ተችሏል።