Wednesday, June 3, 2015

የሰለኽላኻ ከተማ ነዋሪ ህዝብ አምስት ሚልዮን የሚሆን የህዝብ ገንዘብ ለግል ጥቅማቸው አውለዋል የተባሉ አስተዳዳሪዎች ህግ ፊት ባለመቅረባቸው ምክንያት ግንቦት 14 2007ዓ/ም ተቃውሞ እንዳስነሳ ተገለፀ።



       ምንጮቻችን እንደገለፁት- በትግራይ ሰሜናዊ ምእራብ ዞን መደባይ ዛና ወረዳ፤ ሰለኽላኻ ከተማ የሚኖር ህዝብ የወረዳው አስተዳዳሪ የሆነው አቶ ብርሃነና ምክትሉ አቶ ጎይትኦም ገብረሃወሪያ 5 ሚልዮን የሚገመት የህዝብና የመንግስት ገንዘብ  ለግል ጥቅማቸው እንዳዋሉት በህግ ተረጋግጦ እያለ በባለስልጣኑ አስገዳጅነት በነፃ እንዲለቀቁ በመደረጉ ምክንያት ግንቦት 14 /2007 ዓ/ም ምርጫን በተመለከተ ቅስቀሳ ሲያካሄድ ለነበረ የሰሜናዊ ምእራብ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ተወልደን በድንጋይ እንዳባረሩት ታወቀ።
        የህዝቡ ተቃውሞ በምርጫ ዋዜማ በመሆኑ የሰጉት የስርአቱ ባለ ስልጣናት ደግሞ ሁኔታውን ለማረጋጋት ሲሉ ከፌደራል የተላኩት አባይ ፀሃየና ሳሚኤል ገብረዋህድ ከአበይ ወልዱ ጋር በመሆን ነዋሪውን ህዝብ በመሰብሰብ ግለሰቦቹ ነፃ ቢሆንም ምክር ቤት ሰብስበን 20 አመት እንዲታሰሩ አስወስነን በቁጥጥር ስር አስገብተናቸዋል አዲስ ነገር ካለ ግን ከበላይ ባለስልጣኖች ጋር ተነጋግረን መልሱን እንነግራችኋለን በማለት የማደናገሪያ ሃሳብ እንደሰጧቸው ለማወቅ ተችሏል።
    መረጃው በማከል በሙስና የተከሰሱት አስተዳዳሪዎች በነፃ እንዲለቀቁ አድርገዋል የተባሉት የፍትህ አካላት አባዲ መልኩና ወ/ሮ አልማዝ የተባሉት  ሰዎች የህዝቡን ተቃውሞ ለማረጋጋት ሲሉ ለጊዜው እንዲታገዱ ቢደረግም የስልጣናቸውን እድሜ ለማራዘም የሚጠቀሙበት ምርጫ በማለፉ የታሰሩት ባለስልጣኖችን ፈትተው የታገዱትም ወደ ስራቸው ይመልሷቸዋል በሚል እምነት በከተማው ህዝብ ዘንድ የመነጋገሪያ አርእስት ሆኖ እንዳለ መረጃው ጨምሮ አስረድቷል።