Sunday, July 13, 2014

በአክሱም ከተማ እስርቤት ውስጥ ባጋጠመው የማህበራዊ አገልግሎት ችግር ምክንያት በበሽታ የተሰቃዩ እስረኞች ሰኔ 25/2006 ዓ/ም በፖሊሶች ታጅበው ወደ ህክምና በመሄድ ላይ ሳሉ አጃቢዎቹ በመደብደብ መሳርያቸውን ቀምተው እንዳመለጡ የደረሰን መረጃ አመለከተ፣፣



በአክሱም እስር ቤት ውስጥ ንፁሃን ሰዎች ባልዋሉበት ወንጀል በርካታ ወገኖች ታስረው እየተሰቃዩ መሆናቸውን የገለጸው መረጃው፣ እስር ቤቱ ውስጥ ባለው የአመጋገብና የመኝታ ቤት ችግሮች ብዛት ያላቸው እስረኞች ለበሽታ በተጋለጡበት ወቅት ሰኔ 25/2006 ዓ/ም 2 እስረኞች በፖሊስ ታጅበው ወደ ህክምና እየሄዱ በነበሩበት ግዜ  በከተማዋ ብዛት ያለው ህዝብ በሚንቀሳቀስበት  ቦታ ለአጃቢዎቹ በመደብደብ መሳርያቸውን ነጥቀው እንዳመለጡ ለማወቅ ተችለዋል፣፣
         በእስረኞቹ መሳርያቸውን ከተነጠቁት የፖሊስ አባላት ውስጥ።- አስፋው አዲስአለምና ሙሉብርሃን ታደሰ የተባሉት ሲሆኑ ይህ በእስረኞቹ ያጋጠመ ሁኔታ ወደ የበላይ አመራሮች ሪፖርት ባደረጉበት ግዜ ሃላፊዎቹ አውቃችሁ ነው እንዲያመልጡ ያደረጋችሁት፤ መሳርያውም ከሸጣችሁበት አምጡት ብለው እንዳሰርዋቸው ለማወቅ ተችለዋል፣፣
         ፖሊሶቹን በመደብደብ መሳርያቸውን ይዘው ያመለጡ እስረኞች በፖሊስና በደህንነት አባላት እየተፈለጉ ቢሆንም እስካሁን ግን እንዳልተገኙ መረጃው ጨምሮ አስረድተዋል፣፣